Friday, August 17, 2012

የአቶ በረከት ስምዖን ሽሙጥ: ከፍቅሬ ዘለቀው፣ ኖርዎይ


በባራክ ኦባማ አስተዳደር ዘመን ለመጀመሪያ ጊዜ በደቪድ ካምፕ ዋሽንግቶን የዓለም ምግብ ዋስትናና ፖለቲካ ፈተናዎች በሚል ለተዘጋጀው የግንቦት 18፣ 2012 የቡድን ስምንት (G8- summit) የመሪዎች ጉባኤ አምባገነኑ መለስ ዜናዊ በአለቃቸው ተጋብዘው ለመሳተፍ ከውጪ ይጠብቋቸው የነበረውን የኢትዮጵያንን ቁጣ በጓሮ በር ሸሽተው በመግባት በስብሰባው ላይ ዲስኩር እያሰሙ እያሉ ነበር የመላውን ኢትዮጵያ ህዝብ ድምፅ ባነገበ ጀግናና አለኝታችንአበበ ገላው ቁጣ ቀልባቸው ተገፎ ከዕለቱ ጀምሮ ምናልባትም ለፍፃሜ ህልፈተ-ህይዎታቸው በሽታ ተዳርገው፣ ከአንድ ወር በሗላም በገረጣ ፊትና በከሳ ሰውነት በድጋሜ በሜክሲኮ ዋና ከተማ በኢንዱስትሪ በበለፀጉ አገሮች ስብሰባ ላይ ለመጨረሻ ጊዜ የታዩት።

እስካሁንም የእሳቸው ደብዛ መጥፋት በኢትዮጵያዊያን ዘንድ ደስታና ስጋት የተቀላቀለበት ስሜት ፈጥሮ መነጋገሪያ የሆነ ቢሆንም፣ የጠቅላይ ሚኒስቴሩ እንዲህ መሆን ደግሞ በአንድ ግለሰብ ለምትመራ አገር ወይም በህገ አራዊት ለምትተዳደር አገር በአፍሪካ ቀንድ አለመረጋጋትን ሊፈጥር ይችላል በሚሉና ሐሳባቸውን በጊዜያዊ ጥቅምና መረጋጋት ላይ ያተኮሩትን የምዕራባዊያን ወዳጆቻቸውንም ስጋት መፍጠሩ አገር በቀል የዜና አውታሮች ብቻ ሳይሆኑ የዓለም አቀፉንም ትኩረት በመሳብ የዕለት ከዕለት መነጋገሪያ ርዕስ በመሆን ላይ ይገኛል። 

ይህ በእንዲህ እንዳለ የጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ ጤንነትን በሚመለከት ከመንግስት ተብዬው የበረከት ስምዖን ቢሮ እና በአጋሮቹ ጥቂት የግል ጋዜጦችና የኢንተርኔት ድረ-ገፆች የሚወጣው የተምታቱ መረጃዎች በህዝባችን ብቻ ሳይሆን በኢህአዲግ ደጋፊዎች፣ አባሎችና ለጋሾችም ዘንድ አመኔታን ከማሳጣቱ የተነሳ በባራክ ኦባማ ቢሮ የአፍሪካ ጉዳዮች ክፍል ቃል-አቀባይ እንደጠቆሙት ከመለስ መሰወርና መጥፋት ጋር ተየይዞ ብዙ የኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናትን አግኝተው ስለሁኔታው ለማወቅ እንደሞከሩ መግለፃቸውን ዘ-ዋሽንግቶን ታይምስ የተባለ ድረ-ገፅ ኦገስት 13፣ 2012 ባወጣው ፅሑፍ አስነብቧል። ይህ ስጋት የመነጨው የኢትዮጵያ መንግስት መሠረቱን የጣለው በህገመንግስቱ ላይ ሳይሆን በአቶ መለስ ዜናዊ ወይም በጥቂት የህወሓት መሪዎች ላይ መሆኑ አሁን እየተሰማ ያለውን የስልጣን ሽኩቻ ወደ ባሰ ደረጃ ደርሶ ወደ ለየለት የአፍሪካ ቀንድ ቀውስ እንዳያመራ በመፍራት መሆኑ ግልፅ ነው።  

የመገናኛና ህዝብ ግንኙነት ሚኒስቴር  የሆነው የአቶ በረከት ስምዖን ቢሮም የውስጥ ችግሮችንና የአትዮጵያ ህዝብ የተፈጠረውን ቀዳዳ ተጠቅሞ ለተረገጠው መብቱ እንዳይነሳ በመፍራት ተጨባጭነት የሌላቸው መግለጫዎችን በመንዛት ለማደናገር ቢሞክርም፣ ከተቋቋመ ማግስት ጀምሮ የዚህ ዓይነቱን ሸፍጥና ውሸት መንጥሮ በማውጣት ወይም በማጋለጥ እውነቱን ለኢትዮጵያዊያን በማቅረብ ተወዳጅነትና ዝነኝነትን እያተረፈ የመጣው የህዝብ ዓይንና ጆሮ የሆነው የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን፣ የአምባገነኑ መለስ ዜናዊ መታመም ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋ በማውጣት ላቀረበው ዜና የአቶ በረከት ስምዖን ረዳት የሆነው አቶ ሽመልስ ከማል፣ ጠቅላይ ሚኒስቴሩ አልታመሙም ይህ የኢሳት መሠረተ-ቢስ ወሬ ነው በማለት አናንቆ በተናገሩ ማግስት በተቃራኒው ውሽት የተናገሩት እነሱ መሆናቸውን አቶ መለስ ይመሩት በነበረው የ19ኛው የአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ በስብሰባው ላይ ያልተገኙት በህመም ምክንያት መሆኑን የሴኔጋሉ መሪ አስታውቀው ስለ ጤንነታቸውም መልካሙን በመመኘት ነበር ስብሰባውን የከፈቱት። ይህ የበረከት ቢሮ  ከዚህ በፊት የአሜሪካ የአማርኛውን ሬድዮ ድምፅ ስለማፈናቸው በዚሁ ሬድዮ አቶ ሸመልስ ከማል ተጠይቀው በፍፁም አላደረግንም ብለው በተናገሩ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አለቃቸው አቶ መለስ መታፈኑን አረጋግጠው፣ የበለጠ ለማፈን አቅማቸውን እየመረመሩ እንደሆነ መግለፃቸው ይታወሳል።

በዚህ በተደበቀ እውነታ ይፋ መሆን የተደናገጡት የኢትዮጵያ መሪዎች ለመጀመሪያ ጊዜ በማመን አቶ ሐይለማሪያም ደሳለኝ ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ ትንሽ መታመማቸውን ለብሉንበርግ ዜና አውታር ገለፁ። የህወሐት አንጋፋ መስራች የሆኑት አቶ ስብሐት ነጋም ለአሜሪካ ድምፅ ሬድዮ በሰጡት ቃለ ምልልስ አቶ መለስ መታመማቸውን አምነው አሥር ቀናት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ወደ ሥራ ገበታቸው እንደሚመለሱ እርግጠኝነታቸውን ጠቆሙ። ወዲያውኑ በውሸት የተካነው አቶ በረከት ስምዖን “ጠቅላይ ሚኒስቴር መለሰ ዜናዊ ቀላልና መጠነኛ የጤና መታወክ አጋጥሟቸው የነበረ ቢሆንም አስፈላጊው ሀክምና ተደርጎላቸው አሁን በመልካም ጤንነት ላይ ይገኛሉ፣ ላጋጠማቸው የጤና ችግር ረጅም ጊዜ የቆየና ከፍተኛ የሥራ ጫና ምክንያት መሆኑ፣ ይህን ተከትሎም በህክምና ባለሙያዎች የተወሰነ ዕረፍት እንደታዘዘላቸውና እረፍቱን እንደጨረሱም በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ መደበኛ ሥራቸው ይመለሳሉ” ሲሉ ነበር ጁላይ 19፣ 2012 ለአገር ውስጥና ለውጪ ጋዜጠኞች ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት። አቶ በረከት ይህን መግለጫ ይስጡ እንጂ በአትኩሮት ላያቸው እውነታው ይህ እንዳልሆነ በፊት ገፅታቸው ላይ  ይነበብ ነበር። 

በዚህ ወቅት አምባገነኑ መለስ ዜናዊ ተኝቶ ከነበረበት ሴንት ሉክ፣ የካንሰር ሆስፒታል፣ ቤልጄም የተለያዩድፕሎማቲክ ምንጮችን በመጥቀስ የሚወጡት መረጃዎች የሚጠቁሙት ግን አቶ መለስ እጅግ በጣም እንደታመሙና እንዲያውም ሊድኑ እንደማይችሉ ነበር። ላለፉት 21 ዓመታት የተነገሩት የውሸት ትራክ ሪከርዶች ይቅሩና በዚህ ሁለት ወራት ውስጥ የተነገረንን ውሸት እንታዘብ። የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥንም (ኢሳት) የተለያዩ ሁኔታዎችን በማገናዘብና የዓለም አቀፍ ቀውስ ተንታኝ የውስጥ ታማኝ ምንጭ ነው ያለውን ጠቅሶ ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ ከዚህ ዓለም በሞት መለየት ይፋ ማድረግን ተከትሎ እንደፈለጉ በሚዘውሩት የኢትዮጵያ ቴሌቪዝን እንደተለመደው ኦገስት 1፣ 2012 አቶ በረከት ስምዖን ይህ የኢሳት የውሸት ወሬ እንጂ ጠቅላይ ሚኒስቴሩ በተደረገላቸው የሃኪሞች እርዳታ በጥሩ ጤንነትና እረፍት ላይ እንደሚገኙና አሁንም በጥቂት ቀናት ውስጥ ሥራቸውን  እንደሚጀምሩ ነበር የገለፁ። አቶ ስብሐት ነጋም ከአምስት ቀናት በሗላ ከላይ ሲገለፅ ከነበረው በተፃረረ መልኩ ለጀርመን ድምፅ ራዲዮየአማርኛው ክፍል ቃለ ምልልስ፣ አሁን ህገ-መንግስቱን ተቀብለን ነው የምንሄደው በሥልጣን ዝውርውር ላይ ነው ያለነው ሲሉ ተደምጠው እንደነበር ይታወሳል። እንዲህ በሉ የተባሉት የጋዜጠኝነት ስነ-ምግባር ያጡት የግል ጋዜጣ አዘጋጆች ተብየዎች እንደነ አዲስ አድማስም ጠ/ሚኒስቴር መለስ በቤተ-መንግስት እያገገሙ ነው ተባለ በሚል ርዕስ ከአራት ባለስልጣናት ጋር በመነጋገር ሥራ መጀመራቸውንም ሲያስነብብ ኢትዮጵያን ሪፖርተር በበኩሉ ጠ/ሚኒስቴሩበአሜሪካንአገር በሽርሽር ላይ መሆናቸውን ፅፎ ነበር። ዓይን ያወጣ ውሸት ይሏል ይህ ነው። 

የተባሉት ጥቂት ቀናት አልፈው በሌላ ሲተኩ እየተረበሹ የመጡት አቶ በረከት ስምዖን የመጨረሻ በሚመስል መልኩ ከኢትዮጵያዊያን አዲስ ዓመት በፊት ጠ/ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ ሥራቸውን እንደሚጀምሩ አውስትራሊያ ለሚገኘውኤስ.ቢ.ኤስ ራዲዮ ድምፅ ባደረጉት ቃለ-ምልልስ አስታውቀዋል። አቶ ስብሐት ነጋ ከዝነኛው የኢሳት ጋዜጠኛ ሲሳይ አጌና ጋር ባደረጉት የቴሌፎን ውይይት፣ አዲስ አድማስና ኢትዮጵያን ሪፖርተር ያቀረቡት ዜና ደረቅ ውሸት መሆኑን ጠቁመው እርሳቸውም እስካሁን በዓይናቸው እንዳላዩአቸው ተናግረው፣ በአሜረካ ራዲዮ ጣቢያ እስከ አሥር ቀናት ተመልሰው ሥራ ይጀምራሉ ያልኩት ስህተት ነበር ማለታቸውና ከአቶ በረከት ቢሮ የሚወጣው ዜና ሁሉ አንድም እውነትነት እንደሌለው መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ጠንቅቆ ያውቀዋል። አቶ በረከት የሚያቀርቡት ይህ ሁሉ ውሸት ህዝቡ አያውቅብኝም በማለት ሳይሆን፣ ውሸት ሲደጋገም እንደ እውነት ይወሰዳል በሚል ብሂል እንደሆነ ለማንም የተሰወረ አይደለም።

የደደቢት አንበሶች፣ የአሁኖቹ አገር መሪዎች በአምባገነኑ ኮሎኔል መንግስቱ ሐ/ማርያም ያኮረፈውን የትግራይና የቀረውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ድጋፍ ለማግኘት በሬው ወለደ ዓይነት ዜና ለአሥራ ሰባት ዓመታት ሲያሰራጩ ያካበቱትን የውሸት ልምድ አሁንም እንደ መንግስት ተጠያቂነትን ሳይፈሩ መቀጠላቸው ያስገርማል። ዳሩ ግን ማንን ፈርተው!

የኢትዮጵያ ቁርጥ ቀን ልጅ አቶ ታማኝ በየነ በአንድ ወቅት እንዲህ ማለቱ ትዝ ይለኛል “የሕወሓት ባለሥልጣናት ትግል ከጀመሩበት ጊዜ ጀምሮ ሐገሪቱን እስከተቆጣጠሩበት 1983 ዓም ድረስ ገደልን ያሉት የደርግ ሠራዊት ቢደመር፣ ከኢትዮጵያ ህዝብ ቁጥር ይበልጥ ነበር” ሲል። ዶ/ር ብርሃኑ ነጋም በአንድ ስብሰባ ላይ “ኢሕአዲግ ሃገሪቱን እንደ መንግስት ማስተዳደር ከጀመረ ጊዜ ጀምሮ የተወለደውና ያደገው ወጣቱ ትውልድ ለአንድም ቀን እውነት ሳይሰማ በውሸት ታንፆ አደገ” ነበር ያሉት። ኢትዮጵያዊያን ሙስሊም ወንድሞቻችንም የአቶ በረከት የውሸት ፕሮፓጋንዳ ማምረቻ ማሽን የሆነው ኢቲቪ ባደረሰባቸው ገደብ ያጣ ውሸት በመበሳጨት “ኢቲቪ ይዘጋ፣ ኢቲቪ ይዘጋ፣ ኢቲቪ ይዘጋ” በማለት ነበር ተቃውሞአቸውን ሲያሰሙ የነበረው።

ስለዚህ አቶ በረከት ስምዖን ጠ/ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ ከኢትዮጵያዊያን አዲስ ዓመት በፊት ወደ ሥራ የመመለስን ጉዳይ ከጥቂት የዲያስፖራ ግለሰቦች በስተቀር የመንግስትን እውነት የመናገር ትራክ ሪከርድን በማየት የኢትዮጵያ ሕዝብ ያምነናል ሲሉ ተደምጠዋል።
አይነጋ መስሏት
ተፀዳዳች ከቋት፤ እንዲሉ።
ለነገሩማ አቶ በረከት ይህን ተናግረው አንድ ሳምንት ሳይሞላ ኢሳት በሰበር ዜና የፍትህ ሚኒስቴር አቶ መለስን ለመተካት የሚያስችል ህገ-ረቂቅ መዘጋጀቱንና ፓርላማው ህጉን ለማፅደቅ በአስቸኳይ እንደሚጠራ አሳውቆናል አይደል።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!!
ሞት ለጠላቶቿ!!!

ምንጭ :http://ethiofight.blogspot.no/2012/08/blog-post_17.html

No comments:

Post a Comment